Monday 20 May 2013

ህዝባዊ ውይይት በኖርዌይ May 18,2013


ኖርዌይ ኦስሎና አካባቢው የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ቅዳሜ በ18.05.13 ህዝባዊ ውይይት አደረጉ። ውይይቱ በሀገራችን በግፍ ለተገደሉ፤ በእስር ለሚንገላቱና ለፍትህ ለነፃነትና ለዲሞክራሲ ለሚሰቃዩና ለተሰደዱ ወገኖች የህሊና ፀሎት በማድረግ ተጀምሯል። በርካታ ታዳሚዎችም ሰማያዊ ፓርቲ የጠራውን ሰልፍ በመደገፍ ጥቁር ልብስ ለብሰው ተገኝተዋል።

Ethiopians meeting in Norwayውይይቱ የተጠራው በኖርዌይ ለወገን ደራሽ ግብረ ሀይል ሲሆን ያተኮረውም በሚከተሉት ነጥቦች ላይ ነበር፤
1. በውጪ ሀገር የሚኖረው ኢትዮጵያዊ (ዲያስፖራ) በኢትዮጵያ  ፖለቲካ ውስጥ ስለሚጫወተው ሚናና በሀገር ቤት በሰማያዊ ፓርቲ ስለተጠራው ሰላማዊ ሰልፍ
2. ሰላማዊና ሌሎች የትግል ስልቶች በኢትዮጵያ እና ሰማያዊ ፓርቲ የጠራው ሰላማዊ ሰልፍ
3. ወቅታዊው የኢትዮጵያ ፖለቲካ ከመገናኛ ብዙሀን፤ ከሰብአዊና ከዲሞክራሲ መብቶች አንጻር
4. ወቅታዊው የኢትዮጵያ ፖለቲካ ሁኔታና በሀገር ቤት ስለታቀደው የሰማያዊ ፓርቲ ተቃውሞ ሰልፍ
5. የሀይማኖት ነጻነት በኢትዮጵያና ሰማያያዊ ፓርቲ የጠራው ሰላማዊ ሰልፍ  የሚሉት ይገኙበታል።
በነዚህ ወቅታዊና አንገብጋቢ ርዕሶች ላይ ለታዳሚዎች የመወያያ ሃሳቦችንና ገለጻዎችን ያቀረቡት በቅደም ተከተል አቶ አርጋው ያቆብ፤ አቶ ዳንኤል አበበ፤ አቶ ዳባ ጉተማ፤ አቶ ዳሂሎን ያሲን እንዲሁም አቶ ሙሀመድ ሲራጅ ሲሆኑ ዝግጅቱንና ውይይቱን የመሩት ደግሞ አቶ ዳዊት መኮንን ናቸው።
በውይይቱ ላይ በርካታና ዝርዝር ጉዳዮችና ሀሳቦች ተነስተዋል።
በውጪ ሀገር የሚኖረው ኢትዮጵያዊ (ዲያስፖራው) በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ጉልህ ሚና ሊጫወት እንደሚችል አቶ አርጋው በዝርዝ አቅርበዋል። በሚዲያና በቴክኖሎጂ በመደገፍ አገር ውስጥና ውጪ ካሉ ተቃዋሚ ሀይሎች ጋር የመረጃ ልውውጦችንና ቅስቀሳዎችን በማድረግ፤ ለአለም አቀፍ ድርጅቶች አቤቱታን በማቅረብ፤ ሰላማዊ ሰልፎችን በማድረግ፤ በመዋጮ በቁሳቁስና በሞራል ተቃዋሚ ሀይሎችን በመደገፍ፤ ገዢው አካል አለም አቀፋዊ ድጋፍ እንዳያገኝ በማድረግ፤ በሲቪክ ማህበራት በመደራጀት ወዘተ ዲያስፖራው በኢትዮጵያ ለሚደረገው የዲሞክራሲና የነፃነት ትግል ጉልህና ትልቅ ሚና ሊጫወት እንደሚችል አስረድተዋል። በአንፃሩ ደግሞ በሀገር ጉዳይ ላይ የተሳትፎ ማነስ፤ እኔ ምን አገባኝ የማለት፤ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ አፍራሽ ዜናዎችን በማሰራጨትና የወያኔን ፖለቲካ በማራገብ፤ የመኖሪያ ፈቃድ ካገኙ በኋላ ከትግሉ በማፈግፈግ፤ ለግል ጥቅም በመገዛት ከወያኔዎች ጋር በመተባበር ወዘተ ዲያስፖራው ትግሉን ሊያዳክመው እንደሚችል አስገንዝበው ይህን በተመለከታ ተቃዋሚ ሀይሎች ተገቢውን ክትትል እንዲያደርጉ አሳስበዋል።Ethiopian in the Diaspora, meeting in Norway
በሌላ በኩል ደግሞ የሰላማዊ ትግል ስልቶችን በተመለከተ አቶ ዳንኤል እንዳብራሩት፤ በመቶዎች የሚቆጠሩ የሰላማዊ ትግል ማታገያ ስልቶች የሚገኙ ሲሆን ከነዚህም መካከል ዋና ዋና የሆኑት ከሶስት እስከ አምስት የሚጠጉ ስልቶችን ጠቅሰዋል። ከነዚህም መካከል ትብብር መንፈግና ተፅዕኖ መፍጠር ይገኙበታል። በዚህ አጋጣሚ አሁን ያለውን ስርዓት ለመለወጥ ሁለገብ የትግል እንቅስቃሴን መደገፍ ተገቢ እንደሆነ አስገንዝበዋል።
አቶ ዳባ ጉተማ በበኩላቸው ስለዜጎች መፈናቀል፤ ገዢው ፓርቲ የሚቀሰቅሳቸው ፀብ አጫሪ ሁኔታዎች፤ ለፍትህና ለዲሞክራሲ በሰላማዊ መንገድ በሚታገሉ ንፁሀን ዜጎች ላይ ስለሚደርሰው ግድያ፤ አፈና፤ እስር፤ እንግልትና ወከባ፤ በኑሮ ውድነትና በመሳሰሉት በገጠርና በከተማ በህዝቡ ላይ ስለሚደርስ ስቃይ፤ በአሁኑ ወቅት የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት የሚሆኑት ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን መስዋዕት ለማድረግ የቆረጡ መሆናቸው በአጠቃላይ የፖለቲካ መህዳሩ የሚመች እንዳልሆነ፤ እስከዛሬ የኢትዮጵያ ህዝብ ገዢ እንጂ መሪ አግኝቶ እንደማያውቅና ያሁኑ ግን ሲኦል እንደሆነበት በዝርዝርና በተጨባጭ ምሳሌዎች በጣም በርካታ ጉዳዮችን አንስተው ለተወያይ ታዳሚዎች አቅርበዋል። በተጨማሪም ትላንት ካልነበረ ዛሬ እንደሌለ ዛሬ ከሌለ ደግሞ ነገ እንደማይኖር የታወቀ ስለሆነ ለዛሬ በጣም እንድናስብበት አሳስበዋል።
እንዲሁም አቶ ዳሂሎን ያሲን በተለይ በአሁኑ ወቅት ያለውን የኢትዮጵያ ወቅታዊ የፖለቲካ ሁኔታና ሰማያዊ ፓርቲ ስለጠራው ሰላማዊ ሰልፍን አቶ ዳሂሎን እንደመነሻ የምርጫ 97 ሰላማዊ ሰልፍን ካነሱ በኋላ በአሁኑ ወቅት በይፋ ስለተጠራው ስለዚህ ሰላማዊ ሰልፍ ሊኖሩት ስለሚችሉት አሉታዊና አዎንታዊ ገፅታዎች አብራርተዋል። በዋናነትም የሰላማዊ ሰልፉ መጠራት ቢሳካም ባይሳካም ያለውን ጠቀሜታና በንፅፅርም የሚታዩትን ስጋቶች ተንትነዋል።Ethiopians gathered in Norway to discuss current Ethiopian politics
በወቅቱ በኢትዮጵያ ስላለው የሙስሊም ወገኖቻችንን ጥያቄዎችና በገዢ አካል ስለሚደረገው የሀይማኖት መብት ረገጣ በተጨማሪም አሁን ስላለው ችግር መንስኤ ዘርዘር ያለ ማብራሪያ በአቶ ሙሀመድ ሲራጅ ቀርቧል።
ታዳሚዎችም በርካታ አስተያየቶችንና ጥያቄዎችን በማንሳት ከፍተኛ ተሳትፎ የተደረገበት ውይይት አድርገዋል።
በመጨረሻም የወያኔው መሪ መለስ ዜናዊ በጋዜጠኛ አበበ ገላው የተደረገበትን ተቃውሞ አንደኛ አመት በማስታወስ ነፃነት ነፃነት ነፃነት የሚለው መሪ ቃል በህብረት፣ በስብሰባው  መክፈጫ ላይ ተብሎ እንደተጀመረ ሁሉ የእለቱ ስብሰባ  ሲጠናቀቅም  በተመሳሳይ መልኩ ተሰብሳቢዉ  ከመቀመጫቸዉ ተነስተዉ በአንድ ድምፅ ነፃነት! ነፃነት! ነፃነት!  የሚለዉን ቃል አሰምተዋል።
በስብሰባዉ ማጠቃለያ  ተሰብሳቢዉ በጋራ የተስማሙባቸዉን  የሚከተሉትን ሦስት አበይት ሃሳቦች የስብሰባዉ የአቋም መግለጫ በማድረግ የእለቱን ስብሰባ አጠናቀዋል።
1ኛ.በኢትዮጵያ ዉስጥ የሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ መብት፣የፖለቲካና ሃይማኖት ነፃነት፣ እንዲከበር በተጨማሪ የንፁሃን ወገኖቻችንን ከቤት ንብረታቸዉ አፈናቅለዉ ለሞት ያደረጓቸዉን ሰዋችና የመንግስት ባለስልጣናት፣የሃይማኖት መብት ጥያቄ ባቀረቡ ያሰሯቸዉና የገደሏቸዉን ባለሰልጣናት እነዲሁም በኢትዮጵያ በተለያየ ቦታ የፖለቲካ፣የሚዲያና ሲቪክ ማህበራት አባላትና መሪዋችን ያሰሩና ደም ያፈሰሱ የመንግስት ባለስልጣናት ለፍርድ እንዲቀርቡ ጠይቀዋል።
2ኛ.በኖርዌ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ሰማያዊ ፓርቲ የጠራዉን ሰላማዊ ሰልፍ እንደሚደግፉ በጋራ አቋም መግለጫቸዉ አረጋግጠዋል።በተጨማሪ ከአገር ዉጪና በአገር ቤት ያሉ የፖለቲካ፣የሲቪክ፣የሐይማኖት፣ የሴቶችና ወጣቶች መህበራት ሰማያዊ ፓርቲ ለጠራዉ ሰልፍ በተመሳሳይ መልኩ ድጋፍ እንዲያርጉላቸዉ ተሰብሳቢዉ አክለዉ በአቋም መግለጫቸዉ አሳዉቀዋል።
3ኛ.በኖርዌ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን እያንዳንዳቸዉ የፌስቡካቸዉን ፕሮፋይል በማጥቆርና ቀስቃሽ ድጋፍ ሰጪ ፅሑፎችን ለሌለዉ በማሰራጨት፣እንዲሁም በፓልቶክና በሎሎች ብዙሃን ማሰራጫ ድጋፋቸዉን እንደሚሰጡና ሌላዉም ኢትዮጵያዊ በተመሳሳይ ሁኔታ ድጋፉን በመስጠት ሁሉም የዜግነቱን ግዳጅ እንዲወጣ አሳስበዋል።
አንድነት ሃይል ነዉ!!!
ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!!
በኖርዌይ ለወገን ደራሽ ግብረ ሀይል

No comments:

Post a Comment